የቅድመ ጨዋታ ዳሠሳ፡- ቅዱስ ጊዮርጊስ ከደደቢት


የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 12 ሳምንት መርኃ ግብር ተስተካካይ ጨዋታ በነገው ዕለት ይካሄዳል፡፡ የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌደሬሽን የ12ኛ ሳምንት የፕሪሚየር ሊግ መርኃ ግብሮችን በማስተላለፉ ምክንያት ቅዱስ ጊዮርጊስ ከደደቢት የሚያደርጉት ጨዋታ ለሌላ ጊዜ መተላለፉ ይታወቃል፡፡ ይህ በቅዱስ ጊዮርጊስ እና በደደቢት መካከል የሚካሄደው ጨዋታ ነገ (እሁድ) 10 ሰዓት ጅማሮውን ያደርጋል፡፡


ቅዱስ ጊዮርጊስ ከደደቢት 2009 . የእርስ በእርስ ግንኙነት!


2009 . የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሁለቱ ቡድኖች የመጀመሪያ ዙር ጨዋታቸውን ያደረጉት እሁድ ህዳር 11 ቀን 2009 . ነበር። ይህ ጨዋታ 2009 . የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 2 ሳምንት መርኃ ግብር ሆኖ የተከናወነ ሲሆን ፈረሰኞቹ 2–0 በሆነ ውጤት ማሸነፋቸው ይታወሳል።


በዚህ ጨዋታ የፈረሰኞቹን ቀዳሚ ጎል ያስቆጠረው ምንተስኖት አዳነ 23ኛው ደቂቃ ላይ ነበር፡፡ 23ተኛ ደቂቃ በሃይሉ አሰፋ ከግራ ጥላ ፎቅ አቅራቢያ ያሻገረው ኳስ ናትናኤል ዘለቀ በግንባር ሲገጨው በድጋሚ ምንተስኖት አግኝቶት ኳስን በግንባር ገጭቶ ቀዳሚውን ጎል አስቆጥሯል፡፡ እንዲሁም 45 ደቂቃ በድጋሚ በሃይሉ አሰፋ ከማዕዘን ምት ያሻገረው ኳስ አዳነ ግርማ 2ኛውን ጎል በማስቆጠር ጨዋታው በፈረሰኞቹ 2-0 እንዲጠናቀቅ ሆኗል፡፡


ቅዱስ ጊዮርጊስ 2009 . 2 ዙር ጨዋታውን ከደደቢት ጋር ያደረገው ቅዳሜ የካቲት 25 ቀን 2009 . ነበር፡፡ ይህ ጨዋታ የተካሄደው በአዲስ አበባ ስታዲየም ሲሆን በዚህ ጨዋታ ፈረሰኞቹ በአንደኛ ዙር ያላቸውን የበላይነት ደግመዋል፡፡ ጨዋታው በቅዱስ ጊዮርጊስ 3-2 አሸናፊነት ሲጠናቀቅ ጨዋታው በተጀመረ 16 ደቂቃ ላይ ፕሪንስ ሰቬርኒሆ ለሳላሃዲን ሰኢድ ከመስመር ወደ ሳጥን ውስጥ የቀነሰለትን ኳስ ሳላሃዲን ሰኢድ አስቆጥሮ ፈረሰኞቹ መምራት ጀመሩ፡፡ በጨዋታው 31 ደቂቃ ላይ በሃይሉ አሰፋ ከመስመር ያሻገረውን ጥሩ ኳስ ምንተስኖት በአስገራሚ የግንባር ኳስ ፈረሰኞቹን 2-0 እንዲመሩ አስቻለ፡፡ እንዲሁም 50 ደቂቃ ላይ በሀይሉ አሰፋ ከቅጣት ምት ያሻገረውን ኳስ ሳላሃዲን በርጌቾ በግንባር ገጭቶት ኳስ የግቡን አግዳሚ ገጭቶ ሲመለስ ሳላሃዲን ሰኢድ አግኝቶት ጎል በማስቆጠሩ ፈረሰኞቹ 3-0 መምራት ችለዋል፡፡


ኖም ደደቢቶች ከኋላ በመነሳት እና 2 ጎሎችን በማስቆጠር ወደ ጨዋታው ለመመለስ ጥረት ማድረግ ችለው ነበር፡፡ 70 ዲቂቃ ላይ ጌታነህ ከበደ በቅጣት ምት እንዲሁም 72 ደቂቃ ላይ አበባው ቡጣቆ በራሱ ጎል ላይ ባስቆጠረው ጎል ታግዘው ደደቢቶች ልዩነቱን ማጥበብ ችለዋል፡፡ ሆኖም ጨዋታው በቅዱስ ጊዮርጊስ 3-2 አሸናፊነት ተጠናቋል፡፡


የዘንድሮ የውድድር ዓመት ቁጥሮች ስለ ሁለቱ ቡድኖች ምን ያሳያሉ?


ቅዱስ ጊዮርጊስ በያዝነው የውድድር አመት 13 ጨዋታዎችን ሲያደርግ 5 ጨዋታዎችን በአሸናፊነት ተወጥቶ 7 ጨዋታዎችን በአቻ ውጤት ፈጽሞ በአንድ ጨዋታ ላይ ሽንፈትን አስተናግዷል፡፡ ደደቢት በበኩሉ ካደረጋቸው 13 ጨዋታዎች መካከል 8 ጨዋታን በአሸናፊነት አጠናቆ 4 ጨዋታን በአቻ ውጤት ፈጽሞ በአንድ ጨዋታ ሽንፈትን አስተናግዷል፡፡፡፡ በዚህ ውጤት መሰረት ደደቢቶች 28 ነጥብ በመሰብሰብ በፕሪሚየር ሊጉ የደረጃ ሠንጠረዥ 1 ደረጃ ላይ ሲገኙ ቅዱስ ጊዮርጊስ 22 ነጥቦችን በመያዝ 4 ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡


ደደቢት በአዲስ አበባ ስታዲየም ያደረጋቸው ጨዋታዎች ቁጥራዊ ማሳያዎች!


የቅዱስ ጊዮርጊስ ተጋጣሚ የሆነው ደደቢት በያዝነው የውድድር ዓመት በአዲስ አበባ ስታዲየም ያደረገው 9 የፕሪሚየር ሊግ ጨዋታዎችን ነው፡፡ በሜዳቸው ማድረግ ከቻሉት 9 ጨዋታዎች መካከል 6 ጨዋታዎች ላይ ድል ሲቀናቸው፣ 2 ጨዋታ አቻ ተለያይተው በአንድ ጨዋታ ሽንፈትን አስተናግደዋል፡፡ ደደቢት ስፖርት ክለብ 2010 . ባደረጋቸው አጠቃላይ ጨዋታዎች ሽንፈትን ያስተናገደው በአንድ ጨዋታ ላይ ብቻ ነው፡፡ በመሆኑም ይህ ጨዋታ በአንድ ጨዋታ ላይ ብቻ ሽንፈትን ባስተናገዱ 2 ክለቦች መካከል የሚደረግ ጨዋታ ይሆናል፡፡

ደደቢት በአዲስ አበባ ስታዲየም ያሸነፋቸው ክለቦች እና ውጤቶቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡ ሀዋሳ ከነማን 2-1 ሲዳማ ቡናን 5-2 ኢትዮ. ኤሌክትሪክን 3-1 ኢትዮጵያ ቡናን 1-0 እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኚቨርሲቲን 4-1 እና መከላከያን 4-0 ማሸነፍ ችሏል፡፡ ደደቢት በአዲስ አበባ ስታዲየም 2 ጨዋታ አቻ የተለያየ ሲሆን አቻ የተለያው በተመሳሳይ 0-0 በሆነ ውጤት ነው፡፡ ጨዋታዎቹን ያካሄደው ከወላይታ ድቻ እና ከፋሲል ከነማ ጋር ሲሆን በእነዚህ ጨዋታዎች ጎል አላስቆጠረም፤ ጎልም አላስተናገደም፡፡ ይህ ክለብ በያዝነው የውድድር ዓመት በሜዳው የተሸነፈው በጅማ አባ ጅፋር ብቻ ሲሆን ጨዋታው በጅማ አባ ጅፋር 2-1 አሸናፊነት ተጠናቋል፡፡ ደደቢት በአጠቃላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ባካሄዳቸው ጨዋታዎች ላይ 20 ጎል ሲያስቆጥር 7 ጎሎችን አስተናግዷል፡፡

ደደቢት በያዝነው የውድድር ዓመት ከሜዳው ውጪ 4 ጨዋታዎችን ማድረግ ችሏል፡፡ በእነዚህ 4 ጨዋታዎች ላይ 2ጨዋታን ማሸነፍ ሲችል፣ 2 ጨዋታዎች ላይ የአቻ ውጤት አስመዝግቧል፡፡ ደደቢት ከሜዳው ውጪ ተጉዞ ማሸነፍ የቻለው መቐለ ከነማ 2-0 እና አርባምንጭ ከነማን 2-1 በሆነ ውጤት መሆኑ ይታወሳል፡፡ ይህ ክለብ ከሜዳው ውጪ ተጉዞ 2 ጨዋታዎችን በአቻ ውጤት ሲያጠናቅቅ ተጋጣሚዎቹ የነበሩት አዳማ ከነማ እና ድሬዳዋ ከነማ ነበሩ፡፡ ከሁለቱም ክለቦች ጋር በተመሳሳይ 0-0 በሆነ ውጤት ጨዋታውን አጠናቋል፡፡ ደደቢት በአጠቃላይ ከሜዳው ውጪ ባደረጋቸው 4 ጨዋታዎች ላይ 4 ጎሎችን ሲያስቆጥር 1 ጎሎችን አስተናግዷል፡፡


ቅዱስ ጊዮርጊስ ባደረጋቸው 13 ጨዋታዎች 16 ጎሎችን ሲያስቆጥር 6 ጎሎቹን አስተናግዷል፡፡ ደደቢት በበኩሉ 13 ጨዋታዎች 24 ጎሎችን ሲያስቆጥር 8 ጎሎችን አስተናግዷል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊሶች በአማካይ በጨዋታ 1.23 ጎሎችን ሲያስቆጥሩ ደደቢት በጨዋታ በአማካይ 1.85 ጎል እያስቆጠሩ ለዚህ ጨዋታ ደርሰዋል፡፡ በመከላከል ረገድ ቅዱስ ጊዮርጊስ በጨዋታ በአማካይ 0.46 ጎሎችን ሲያስተናግድ ደደቢት በጨዋታ በአማካይ 0.61 ጎል አስተናግዷል፡፡


የደደቢት የጨዋታ አቀራረብ!


የአሰልጣኝ ንጉሴ ደስታ ስብስብ የሊጉ ጅማሬ ላይ የአቻ ውጤቶችን በተደጋጋሚ እያስመዘገበ ቢቆይም በፍጥነት ውጤት ወደመሰብሰብ ተሸጋግሯል፡፡ ለዚህም ማሳያ የሚሆነው ካለፉት 8  ጨዋታዎች መካከል 7 ጨዋታዎችን ማሸነፍ መቻሉ ነው፡፡


ይህ ጨዋታ በሊጉ ጠንካራ የፊት መስመር ያለው እና ጠንካራ የተከላካይ ክፍል ያላቸው ክለቦች የሚያደርጉት ትንቅንቅ ነው፡፡ ደደቢት ካስቆጠራቸው 24 ጎሎች ውስጥ 14 ጎሎችን ያስቆጠሩት 2 ተጨዋቾች ናቸው፡፡ ምንም እንኳ ደደቢት ካስቆጠራቸው ጎሎች ውስጥ 9 ጎሎችን ያስቆጠረው ጌታነህ ከበደ በቅጣት ምክንያት የዚህ ጨዋታ አካል ባይሆንም ሌላኛው የክለቡ ወሳኝ የመስመር አጥቂ አቤል ያለው የዚህ ጨዋታ አካል ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በዚህኛው በኩል የቅዱስ ጊዮርጊስ የተከላካይ ክፍል ባለፉት 13 ጨዋታዎች ላይ ያስተናገደው 6 ጎል ብቻ ነው፡፡


ደደቢት ባለፉት አመታት ቅዱስ ጊዮርጊስን የሚፈትን ቡድን መስራት አልቻለም፡፡ ለዚህም ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር በተገናኘበት ጨዋታዎች በተከታታይ ሽንፈትን አስተናግዷል፡፡ ሆኖም የአሰልጣኝ ንጉሴ ደስታ ስብስብ በቀላሉ ለቅዱስ ጊዮርጊስ እጁን ይሰጣል ተብሎ አይጠበቅም፡፡ ለዚህም ክለቡ ባለፉት ጨዋታዎች ያካበተው የአሸናፊነት ስነ ልቡና በጨዋታው ላይ ጠንካራ ተፎካካሪ ያደርገዋል ብሎ ይጠበቃል፡፡ ከዚህ ጎን ለጎን ቅዱስ ጊዮርጊስ እያሳያ ካለው ደካማ አቋም አንጻር ደደቢት በዚህ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስን ይፈትናል ብሎ ይጠበቃል፡፡ የ3 ወራት ቅጣት ከኢትዮጵያ እግርኳስ ፌደሬሽን የተጣለባቸው አሰልጣኝ ንጉሴ ደስታ በቅርብ ሳምንታት ባደገጓቸው ጨዋታዎች ላይ 4-3-3 የጨዋታ ፎርሜሽንን ይዘው ወደ ሜዳ መግባታቸውን ተመልክተናል፡፡ በቅጣት ላይ የሚገኙት አሰልጣኝ ንጉሴ ይህንን ጨዋታም በሜዳ ተገኝተው ቡድናቸውን አይመሩም፡፡


ደደቢት ባለፉት ጨዋታዎች ላይ 4-3-3 የጨዋታ ፎርሜሽንን ሲተገብር ሲጠቀማቸው የነበሩትን ጨዋታዎች ባሳለፍነው ሳምንት ላይ ከጉዳት እና ከቅጣት ጋር በተያያዘ ለውጥ አድርጓል፡፡ በዚህም ደደቢት መከላከያን 4-0 ሲያሸንፍ  የተጠቀማቸው ተጨዋቾች የሚከተሉት ናቸው፡፡


ግብ ጠባቂ፡- አማራህ ክሌመንት

ተከላካዮች፡- ስዩም ተስፋዬ፣ ደስታ ደሙ፣ ኩሊባሊ ከድር፣ ብርሃኑ ቦጋለ

አማካዮች፡- የአብሥራ ተስፋዬ፣ አስራት መገርሳ፣ ፋሲካ አስፋው

አጥቂዎች፡- ሽመክት ጉግሳ፣ አክዌር ቻሞ፣ ኤፍሬም አሻሞ


ደደቢት ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር በሚያደርገው ጨዋታ ከጉዳት በተመለሱ ተጨዋቾች ጋር በተያያዘ የተጨዋች አጠቃቀም ለውጥ ሊያደርጉ ይችላሉ፡፡ በዚህም አቤል ያለው ወደ ጨዋታ ተመልሶ የአጥቂ መስመሩን የሚቀላቀልበት ዕድል ይኖራል፡፡ እንዲሁም በቀደሙት ጨዋታ በግራ መስመር ላይ ሲጠቀሙት የነበረው ሰለሞን ሀብቴን ባሳለፍነው ጨዋታ ብርሃኑ ቦጋለ ተክቶት መግባቱ ይታወሳል፡፡ እንዲሁም ክለቡ ከመከላከያ ጋር ባደረገው ጨዋታ ላይ በ4-3-3 የጨዋታ ዘይቤ የቡድኑ የአጥቂ አማካይ ሆኖ ተሰልፎ የነበረው አቤል እንዳለ በፋሲካ አስፋው እንደተተካ ተመልክተናል፡፡ በተጨማሪም ክለቡ ከመከላከያ ጋር ጨዋታውን ሲያደርግ በጉት ምክንያት ከሜዳ የመጣውን አስራት መገርሳን አቤል እንዳለ እንደተካው ይታወቃል፡፡


በአጠቃላይ ደደቢት 4-3-3 የጨዋታ ዘይቤን ለረጅም ሳምንታት ሲጠቀም ቆይቷል፡፡ ደደቢት ይህንን የጨዋታ አቀራረብ ሲቀይር ወደ ቀጥተኛ 4-4-2 ፊቱን ያዞራል፡፡ ይህም የሚሆነው ጨዋታው ያለ ጎል ከሄደ እና ደደቢቶች በጨዋታው ላይ ጎል ለማስቆጠር ሲፈልጉ ነው፡፡ አሰልጣኝ ንጉሴ ደስታ 4-3-3 ወደ 4-4-2 ፊቱን ሲያዞር 2 የአጥቂ አማካዮች አንዳቸውን ሆኖም በብዛት አቤል እንዳለን አስወጥቶ ኤፍሬም ኣሻሞን ያስገባል፡፡ በመቀጠል አቤል ያለው በፊት አጥቂነት ከጌታነህ ከበደ ጋር ይሰለፋል፡፡ በዚህም የጨዋታ ፎርሜሽኑን ቅርጽ ለውጠው 2 አጥቂ ይጫወታሉ፡፡


ደደቢት የኳስ ቁጥጥር ብልጫን ለመውሰድ እና ኳስን ለመመስረት የሚሞክር ሰብስብ አይደለም፡፡ ቡድኑ ቀጥተኛ ኳሶችን መጫወት የሚፈልግ ሲሆን ከወገብ በላይ ባለው የሜዳ ክፍል የተጋጣሚ ቡድን ተጨዋቾችን ስህትት በሚገባ የሚጠቀሙ ተጨዋቾች ያሉበት ክለብ ነው፡፡ ደደቢቶች ኳሶች በራሳቸው የሜዳ ክልል እንዲቆዩ አይፈቅዱም፡፡ በፈጣን ቅብብል ተጋጣሚ ሜዳ ለመግባት ይሞክራሉ፡፡ በዚህ የጨዋታ ዕቅድ ኳሶቹ በተጋጣሚ ሜዳ ላይ ሲደርሱ በፍጥነት ወደ መስመር ወጥተው ወደ ሳጥን ውስጥ እንዲሻገሩ ይሆናሉ። ከዚህ ጎን ለጎን የቡድኑ የአጥቂ አማካዮች ወደ ሳጥን የቀረበ ቦታ አያያዝ ቡድኑ በመስመሮች መካከል ያሉትን ክፍተቶች እንዲጠቀሙ እገዛ ያደርጋል፡፡


በዚህ የጨዋታ ዕቅድ በብዛት የሜዳውን የቀኝ ክፍል የሚመርጥ ቡድን ነው። በቀኙ የሜዳ ክፍል ስዩም ተስፋዬ እና ሽመክት ጉግሳ በጥልቀት የማጥቃት ሂደት ላይ ይሳተፋሉ። በጨዋታ እንቅስቃሴ በግራ መስመር አጥቂነት የሚሰለፍ አቤል ያለው ሜዳውን አጥብቦ በፍጹም ቅጣት ምት ሳጥን ውስጥ ይገኛል፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ ደደቢት በሳጥን ውስጥ 2-3 ተጨዋቾች ይኖሩታል፡፡ በተደጋጋሚም የተጋጣሚ ቡድን 2 የመሃል ተከላካዮች 2 የደደቢት አጥቂዎች ጫና ሲደርስባቸው ይታያል፡፡


ደደቢት በአንፃራዊው በሜዳው የግራ መስመር ላይ ያለው ተሳትፎ አናሳ ነው። ለዚህም የግራ መስመር ተከላካዩ የቡድኑ የመከላከል ሚዛናዊነት ለመጠበቅ በራሳቸው ሜዳ በመቅረቱ የሚከሰት ነው፡፡ በዚህም የግራ መስመር ተከላካዩ ሰለሞን ሀብቴ/ ብርሃኑ ቦጋለ በራሱ ሜዳ በመቅረት የደደቢትን የመጨረሻ ተከላካዮች ቁጥር 3 ያደርሳሉ።


ደደቢቶች የተጋጣሚ ቡድን ተከላካዮች ወደ መሃል ሜዳ ለመሳብ በተደጋጋሚ ይሞክራሉ፡፡ በዚህም ከፊት መስመር ያሉ 3 አጥቂዎቻቸውን ፍጥነት ለመጠቀም ይረዳቸዋል፡፡ በተለይም ደደቢት 1 ጎል ካስቆጠረ ደጋግሞ ጎል ለማስቆጠር እና የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር የሚቸገር ክለብ አይደለም፡፡ ተጋጣሚ ቡድን ጎል ሲቆጠርበት የተጋጣሚ ቡድን ተከላካዮች ወደ መሃል ሜዳ ተጠግተው ለመጫን ይሞክራሉ፡፡ በዚህ ሂደት በተጋጣሚ ቡድን ተከላካዮች እና በግብ ጠባቂው መሃል ያለው ክፍተት ይሰፋል፡፡ ይህ ክፍተት መስፋት ለደደቢቶች እጅጉን የሚመች ነው፡፡ ኤፍሬም አሻሞ፣ ሽመክት ጉግሳ እና አቤል ያለውን የሚይዘው የአጥቂ ክፍል የተጨዋቾቹን ፍጥነት በተደጋጋሚ ሲጠቀም ይታያል፡፡


ደደቢት ከመከላከያ ጋር ባደረገው ጨዋታ በጌታነህ ከበደ መቀጣት ምክንያት ይህንን ተጨዋች ተክቶ ወደ ሜዳ የገባው አክዌር ቻሞ በጨዋታው ላይ ጥሩ እንቅሳቄ ሲያደርግ ተመልክተናል፡፡ ይህ ኢትዮጵያዊ ተጨዋች የተሰጠውን የፊት አጥቂነት በሚገባ ተወጥቷል፡፡ በጨዋታው ላይ 2 ጎሎችን አስቆጥሯል፡፡ በጨዋታው ላይ ጥሩ እንቅስቃሴ ሲያደርግም ታይቷል፡፡ ከቡድን አጋሮቹ ጋር ያለው ግንኙነት ማራኪ ነው፡፡ ከኳስ ውጪ የቦታ አያያዙ እና ኳሶችን የሚቀበልበት መንገድ ተጨዋቹ ትኩረት እንዲሰጠው ያደርጋል፡፡ ከፍጹም ቅጣት ምት ክልል ውጪ የሚመታቸው ኳሶች ኢላማቸውን የጠበቁ ናቸው፡፡ እንዲሁም በፍጹም ቅጣት ምት ክልል ውስጥ የሚነካቸው ኳሶች የተሳኩ መሆኑን ታዝበናል፡፡


በፈረሰኞቹ ቤት ያሉ ጉዳቶች!

በዚህ ሰዓት በቅዱስ ጊዮርጊስ ስብስብ ውስጥ በጉዳት ላይ የሚገኘው ናትናኤል ዘለቀ ብቻ ነው፡፡ ከናትናኤል ዘለቀ ውጪ ያሉ ተጨዋቾች ለዚህ ጨዋታ ዝግጁ መሆናቸውን ሰምተናል፡፡


እናሸንፋለን፣
በሳንጃው ሙሉ እምነት አለን!

Comments

Popular posts from this blog

የቅድመ ጨዋታ ዳሠሳ፡- ወልድያ ከቅዱስ ጊዮርጊስ